Saturday, April 28, 2012

የት ፈጨሺው?

(ጌታቸው አሰፋ፤ ሚያዝያ 13 ቀን  2004 ዓ.ም.) በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በጾም ጊዜ የፍስክ ምግቦች ስም መጠራት የለበትም በሚል እሳቤ ላይ የተመሰረተ የልጆች (የወንድም የሴትም) ጨዋታ አለ። አንድ ልጅ ድንገት ተሳስቶ የፍስክ ምግብ ስም ከጠራ ሌሎች ልጆች ተሽቀዳድመው በቁንጥጫ ይይዙታል። ተቆንጣጩ ጾሙ ሲፈሰክ ለቆንጣጩ የሚሰጠውን የፍስክ ምግብ ጠርቶ ቃል ካልገባ አይለቀቅም። በዚህም ምክንያት ልጆቹ በጾም ወቅት ወሬ ሲያወሩ የፍስክ ነገር እንዳያነሱ መጠንቀቅ አለባቸው ማለት ነው። ይህን የፍስክም የጾምም ምግቦችን የሚያነሳው ጽሑፍ ለመጻፍ አስብ የነበረው ታላቁ የሁዳዴ ጾም ባለፈው ሳምንት ከመጠናቀቁ በፊት ነበር። ይሁንና የአንባቢያን ቁንጥጫ ፈርቼ ሳይሆን አዲስ ጉዳይ የቆየ ጉዳይን እየገፋብኝ ጾሙ ካለቀ በኋላ እነሆ ዛሬ ለመጻ(!) በቅቷል። እንቀጥል።

ኑ መረጃን እንሰብስብ፤ ተደራሽም እናድርገው


(ጌታቸው አሰፋ፤ መጋቢት 29 ቀን  2004 ዓ.ም.) ሰሞኑን በዝቋላ አቦ ገዳም ዙሪያ ያለውና አንድ ለአካባቢው የሆነው (ለአንድ ለእናቱ እንዲሉ) ግርማ ሞገሳሙ ደን በአሳዛኝ ሁኔታ ሲቃጠል ነበር (በጎግል ኧርዝ ካርታ ላይ ደኑን ፍንትው ብሎ ብታዩት አንድ ለአካባቢው የመሆኑ ነገር እጅግ ያሳሳችኋል)።ብዙ ሰው ከአዲስ አበባም ከደብረዘይትም እየተጠራራ ሄዶ ተጋግዞ አጠፋው - በእግዚአብሔር ቸርነት። ይሄ ነገር ከአሁን በፊት የተደጋገመ ክስተት በመሆኑ ለወደፊትም አንድ ነገር ካልተደረገ እንደገና ኧረ ከዛም በላይ ላለመከሰቱ ምንም ዋስትና የለም። እንደገና እንዳይከሰት ለማድረግ የተለያዩ ነገሮች መደረግ እንዳለባቸው በየቦታው ያለ ሰው ሲወያይ ነበር።