Sunday, November 25, 2012

በሌለ በሬ ማረስ?


(ጌታቸው አሰፋ፤ ኅዳር 15  ቀን  2004 ዓ.ም.)ስለ ‘ያ ትውልድ’ና ‘ይሄ ትውልድ’ ከመጻፍ አስቀድሞ ‘ያ ትውልድ እና ይሄ ትውልድ ስንል ምን ማለታችን ነው?’ የሚለውን ጥያቄ መመለስ ተገቢ ነው። በተለመደው አባባል በ1960ቹ መጀመሪያ አጋማሽ ውስጥ ይካሄዱ በነበሩት የተማሪዎች እንቅስቃሴዎች ወቅት እድሜያቸው ቢያንስ ለአቅመ-መሳተፍ የደረሱ ሰዎች ስብስብን ነው ‘ያ ትውልድ’ የምንለው።
ላላ ስናደርገው ….የእድሜ መስፈርቱ እንዳለ ሆኖ ቀጥሎ ያለውን አይነት ግጥም የሚገጥም ሰው ወይም እንዲህ ተብሎ የተጻፈ ግጥምን ማንበብ አሁን ድረስ የሚመስጠው ሰው አባል የሆነበት ትውልድ ማለት ነው ልንልም እንችላለን።

ኦባማና የእጅ ነሺዎች አሜሪካ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ኅዳር 7  ቀን  2004 ዓ.ም.)የአሜሪካው ምርጫ እነሆ ተጠናቀቀ። ፕሬዚደንት ኦባማ ለሁለተኛ ጊዜ ተመርጠዋል። አንቱ የተባሉ ተንታኞች፤ ዋና ዋና የቅድሚያ ግምቶች የሚሰጡ ክፍሎች ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚቻልበት ደረጃ ምርጫውን ማን እንደሚያሸንፍ ለመተንበይ አለመቻላቸው ግልጽ ነበር (ከናቲ ሲልቨር በስተቀር)። መጨረሻ ላይ አሸናፊ ሲታወቅም በጣም በትንሽ ልዩነት እንደሚሆን ሲናገሩ ነበር።

ባለሦስት ስለቱ ኸሪከን


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥቅምት 30  ቀን  2004 ዓ.ም.)በአሜሪካና በካናዳ ምስራቃዊ ዳርቻ ከተሞች የዚህ ሳምንት ሰኞና ማክሰኞ እንደወትሮው አልሆኑም። በብዙኃን መገናኛዎች እንደተከታተላችሁት ሳንዲ ተብሎ በሚጠራው ጋላቢ ማዕበል(ኸሪከን) ሚልዮኖች ለችግር ተጋልጠዋል። በውሃ ነፋስ እና እሳት ስለት ጉዳት ደርሶባቸዋል። በአትላንቲክ ውቅያኖስ አካባቢ የሚከሰተውና ከፍተኛ ፍጥነት ያለው ማዕበል ‘ኸሪከን’ ተብሎ ይታወቃል።

ይድረስ ለመንግሥት- ሞያ በልብም በግልጽነትም ነው።


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥቅምት 23  ቀን  2004 ዓ.ም.)እነሆ አባያችንን ለመደገብ የተጀመረው ታላቅ ፕሮጄክት ደጋፊም ነቃፊም የሚለውን እያለ ባሳለፈበትና ባለበት ሁኔታ ከአስር በላይ ወይም በትክክል ለመግለጽ አስራ አንድ ፐርሰንት ያህሉ መጠናቀቁን መንግሥት እየተናገረ ነው። በሀዘንም በደስታም ምክንያት ለአንድም ቀን ቢሆን ስራው ሳይቋረጥ እየቀጠለ መሆኑን ተነግሮናልና - ደስ ይላል። ደስታችንን እያጣጣምን መነሳት ያለበትን እናነሳለን።

ግብርናችን


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥቅምት 16  ቀን  2004 ዓ.ም.) በአጼ ኃይለሥላሴ ትተዳደር የነበረችው ኢትዮጵያ ሀያ ሰባት ሚልዮን ህዝብ ነበራት።  ከሃያ አንድ ዓመታት የዙምባቤ ቆይታ በኋላም ባለቤታቸውን ‘ጓድ ውባንቺ ቢሻው፤’ ብለው የሚጠሩት መንግሥቱ ኃይለማርያም የአገሪቱ ርእሰ ብሄር የነበሩ ጊዜና ኢሰፓን በመሰርቱበት ዓመት አካባቢ  ደግሞ ኢትዮጵያዊያን አርባ ሚልዮን ገደማ ነበርን። ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም የተረከቧት አገር ደግሞ ቢያንስ ሰማንያ ሚልዮን ሰዎችን ይዛለች።

ፍሰትና ብክነት


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥቅምት 9  ቀን  2004 ዓ.ም.) በአንድ አገር አዛላቂ የምጣኔ ሀብታዊ ክንውንውታ ላይ ወሳኝ ሚና የሚጫወቱ ፍሰቶች አሉ። እዚህ ውስጥ የምናካትታቸው የቁስ፤ የመረጃ፤ የኃይል፤ የገንዘብ እንዲሁም የእንስሳት የእጽዋትና የሰው ፍ(ል)ሰት ናቸው። እነዚህን ፍሰቶች በተገቢው መጠን ቦታና ጊዜ መጠቀም ስንችል ነው በምጣኔ ሀብታችን ላይ የሚኖራቸው በጎ ተጽእኖ ማጉላት የሚቻለው። አለበለዚያ ብክነት ይከተላል። እስቲ አንድ በአንድ እንያቸው።

‘አረንጓዴ’ አብዮት


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥቅምት 2  ቀን  2004 ዓ.ም.) ዓለማችን ከፓለቲካዊ አብዮቶች (መነሻ ቃል፡ አበየ - ‘እምቢ አለ’) በተጨማሪ ሌሎች ዘመን ቀያሪ፤ ሂደት ለዋጭ አብዮቶችን  አስተናግዳለች - የግብርና አብዮት ፤ የኢንዱስትሪ አብዮት ፤ የሳይንስ አብዮት፤ የዲጂታል አብዮት። እነዚህ አብዮቶች ‘አብዮት’ ያሰኛቸው ከዛ በፊት ግብርና ወይም ኢንዱስትሪ ወይም ሳይንስ ወይም ዲጂታላዊ እንቅስቃሴ ወይም ስራ ስላልነበረ አይደለም። በመጠናቸውና በአይነታቸው ከተለመደውና ከነበረው አሰራርና አካሄድ ለየት ባለ መልኩ ሁኔታ ቀያሪ በሆነ መገለጫ ግብርናው፤ ኢንዱስትሪው፤ ሳይንሱና የመረጃ ቴክኖሎጂው ስለተስፋፋና አገሮች ከተለመደው መንገድ ‘በእምቢታ’ ወጥተው ወደ አዲሱ መንገድ ስለገቡ ነው ከአብዮት ጋር ተያይዞ የሚነገርላቸው።

አፕል እና አካባቢ


(ጌታቸው አሰፋ፤ መስከረም 25  ቀን  2004 ዓ.ም.) እነሆ አዲሱ ትውልደ-አይፎን iPhone 5 ገበያ ላይ ውሏል። በየአገሩ በየከተማው ከሰው ሁሉ አስቀድሞ ለመግዛት የነበረው ወረፋ በአንዳንድ የምግብ እጥረት ባለባቸው አገሮች ለምግብ ነው እንዴ ያስብል ነበር። በምእራቡ ዓለም ደግሞ በነጻ የሚታደል ነገር አለ እንዴ (መቼም እንደ ፈረንጅ በነጻ የሚታደል ነገርን ለመቀበል በነጻነት የሚሰለፍ አይቼ አላቅም)። 

የህልም መስመረኛ


(ጌታቸው አሰፋ፤ መስከረም 18  ቀን  2004 ዓ.ም.) በኢትዮጵያዊነቴ እንድኮራ የሚያደርጉኝ ብዙ በርካታ ነገሮች አሉ። አንዱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው (አንዴ ሳይሆን በተደጋጋሚ ያየሁት የአስተናጋጆቹ ለራሳቸው አገር ሰው ያላቸው ከተገቢ በታችና አሳፋሪ መስተንግዶና አያያዝ እንዳለ ሆኖ ማለት ነው)። የዛሬ ጽሑፍ ማጠንጠኛ ስለ ኩራት እንጂ ስለ ሀፍረት አይደለም። አየር መንገዳችን ከዘመን ዘመን በተሻገረ ቁጥር ከእድገት ወደ እድገት የሚሸጋገር፤ ማለም የማያቆም፤ አልሞም የሚፈጽም፤ በአቻነት መነጋገር፤ በአብሮነት መስራት የሚችል፤ለሌሎች አገሮች የሚተርፍ አቅም የገነባ ነው - ደስ ሲል። በቅርቡ ድሪምላይነር (የህልም መስመረኛ) ተብሎ የሚታወቀውን ዘመናዊውን ቦይንግ 787 አውሮፕላን ገዝቶ በመረከብ ከዓለም አየር መንገዶች ሦስተኛ ሲሆን፤ በአገር ደረጃ ደግሞ ከጃፓን ቀጥሎ አገራችን ሁለተኛ ሆናለች።

በ2004 ዓ.ም.ጣራ ስር


(ጌታቸው አሰፋ፤ መስከረም 11  ቀን  2004 ዓ.ም.) እነሆ 2004 ዓ.ም. አለቀ።  ዓመቱን ከኢትዮጵያና ከዓለም የኃይልና የአካባቢ ጉዳዮች አኳያ በግርድፉ እንቃኘው።

‘ብርቱው የአፍሪካ ተደራዳሪ - አፍሪካ በበርካታ ግንባሮች ታጣዋለች።’


(ጌታቸው አሰፋ፤ መስከረም 4  ቀን  2004 ዓ.ም.) በዚህ ሳምንት በሞት የተለዩንን ክቡር አቶ መለስ ዜናዊን ከአዛላቂ ልማት አኳያ የነበራቸውን ሚና በጥቂቱ በማንሳት አስባቸዋለሁ።እንደአለመታደል  ሆኖ እሳቸውም ሳይጽፉ ስላረፉ ወይም በሌሎች ስለሳቸው የተጻፉት ነገሮችም ቢሆኑ በስልጣን ላይ በነበሩበት ዘመን የዕለት ተዕለት ውሎዋቸውን በሚያሳይ መልኩ በዝርዝር አይደለም። እናም ይህን ስጽፍ የምጠቀምባቸው ምንጮች በስራ ዓለም ካወቅኋቸው አጋጣሚዎች በመነሳት ነው።

ስለጅምላ በጅምላ ለጅምላ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጳጉሜን 3  ቀን  2004 ዓ.ም.) አዲስ አበባ በጣም ሰፍታለች። በርካታ መንገዶች ተሰርተዋል እየተሰሩም ነው - በማሳለጫዎችና በመሽሎኪያዎች እንዲሁም በመንገደ-ብዙ ድልድዮች እየተደገፉ ነው። የመኪኖች ቁጥርም እንዲሁ። የመጓጓዣ ችግር ግን አሁንም እንዳለ ነው። በቁጥርና በጥራት የሚገለጽ። በተለየ በተወሰኑ መስመሮችና ጊዜያት። የየራሳቸውም ሆነ የየመስሪያቤታቸው መኪኖች ከሚያሽከረክረውና  በአንጻራዊነት ጥቂት ከሚባለው የአዲስ አባባ ነዋሪ ውጪ ያለው ሰው ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ራሱንና ቁሱን ለማጓጓዝ የሚጠቀመው በጅምላ መጓጓዣዎች ነው። የጅምላ መጓጓዣ ውስጥ ውይይት ታክሲዎች፤ ሚኒ ባስ ታክሲዎች፤ ከኮንትራት ውጪ የሚሰሩ ትንንሽ ታክሲዎች፤ ሎንቺናዎች፤ የአንበሳ አውቶብሶችና የሃይገር አውቶብሶች ይካተታሉ። በቅርቡ በአዲስ አበባ ስራው የተጀመረው የቀላል ባቡር መጓጓዣም የዚህ ክፍል ዋና አካል ነው።

ክረምትና በጋ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ነሐሴ 19  ቀን  2004 ዓ.ም.) የአገራችን የደንና አረንጓዴ ሽፋን ጉዳይ ክረምት ክረምት ሲታይ አማን ይመስላል።  ለወትሮው ራሰ በራ የሚመስለው የሰሜኑ ሜዳና ሸንተረርም ሳይቀር በስሱም ቢሆን በአረንጓዴ ቀለም የተቀባ እንዲመስል የሚያደረገው ክረምት ነው።  ክረምት ከበጋ አገር ምድሩ ሁሉ አረንጓዴ ማድረግ እንኳን ባይቻል እና ባይጠበቅም ቢያንስ ትንሽ የማይባል የአገሪቱ ክፍል ወጥ የሆነ የደንና የሌላ አረንጓዴ ሽፋን እንዳይኖረው የሚደረግበት ምክንያት ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም። ውኃና አልሚዎችን እስካለን ድረስ ይቻላል።

‘በረከተ መርገም’

(ጌታቸው አሰፋ፤ ነሐሴ 12  ቀን  2004 ዓ.ም.) ርዕሱን የተዋስኩት ተወዳጁ የስቶክሆልሙ ኃይሉ ገብረዮሐንስ ወይም ኃይሉ ገሞራው ከዛሬ አርባ አምስት ዓመታት በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ በነበረበት ወቅት ከጻፈውና  ‘በረከተ መርገም’  የሚል ርዕስ ከነበረው ግጥሙ ነው። ኃይሉ ገሞራው ደራሲ፤ገጣሚና ባለቅኔ ነው።  በ‘በረከተ መርገም’ ያኔ ድሮ ያኔ በዓለማችን በተለያየ ዘመን በተለያየ ቦታ ስለ ተፈለሰፉት የቴክኖሎጂ ውጤቶች አንድ በአንድ ፈልሳፊዎቹንም እያነሳ ከተፈጠሩበት ዓላማ ጀርባ ስላላቸው ወይም ሊኖራቸው ስለሚገባው ኅብረተሰባዊ ጠቀሜታ እየጠቆመ ቴክኖሎጂ  በአግባቡ ስንጠቀምበት በረከት ነው በድሃውና በሀብታሙ፤ በተማረውና ባልተማረው፤ በከተሜውና በገጠሬው፤ ‘ባለው’ እና ‘በሌለው’ መካከል ሰፊ ልዩነት የሚፈጠርና ልዩነቱንም በጣም እያሰፋ የሚሄድ ከሆነ  ደግሞ መርገም ነው ይላል። በኃይሉ ገሞራው ‘በረከተ መርገም’ የትችት ስለት የሚተለተሉት በኅብረተሰባዊ ክፍሎች መካከል ያለን ልዩነት በማስፋት አንዱ ወገን ለሌላው ወገን ባርያና አገልጋይ እንዲሆን የሚያደርገው ቴክኖሎጂ ብቻ ሳይሆን ቴክኖሎጂውን የፈጠረውም ሰው ጭምር ነው። 

ከአይበሰብሴው ከረጢት ወደ ዘንቢል- ዘንበል


(ጌታቸው አሰፋ፤ ነሐሴ 5  ቀን  2004 ዓ.ም.) በካናዳ ቶሮንቶ ከተማ በቅርቡ የፕላስቲክ ከረጢት መጠቀምን የሚከለክል ህግ ወጣና መነጋገሪያ ሆነ - በጥቅሙና ጉዳቱ ዙሪያ።  ይህ ከመሆኑ ከአምስት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ስስ ፌስታሎችን የሚከለክል ህግ አወጣች። በየካቲት 5 1999 በነጋሪት ጋዜጣ ላይ በወጣውና አዋጅ ቁጥር 513/1999 ተብሎ በሚታወቀው ይህ ‘የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ አዋጅ’ አንቀጽ ስምንት ንዑስ አንቀጽ 1 እስከ 3 ላይ የፕላስቲክ ከረጢቶች በተመለከተ እንዲህ ይላል፤

‘አዲስ አበባን ያጸዳ የጸዳ ዋጋ ከአምላኩ’


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 28  ቀን  2004 ዓ.ም.)ሰኔ ላይ አንስተነው ወደነበረው የአዲስ አበባ ጽዳት ጉዳይ ተመልሰን መጥተናል። የጽዳት ስራውን የሚፈጽም፤ ክትትል ለሚያደርግ፤ የተሻሉና አዳዲስ አዛላቂ ሃሳቦች የሚያፈልቅ የሰው ኃይል ያስፈልጋል። እዚህ ላይ ነው እንግዲ አብያተ እምነት የሚመጡት - የተከታዮቻቸውን የጊዜ፤ የጉልበት፤ የእውቀትና የገንዘብ ሀብት ይዘው። አዲስ አበባ ውስጥ ያሉት አብያተ እምነት ቁጥራቸው በርካታ ነው። አነሰም በዛም በየቤተ እምነቱ በመደበኛነት የሚገለገለው ተከታይ ቁጥር ጠቅላላ ድምር ቀላል አይደለም - ኢመደበኛውን ሳንቆጥር።

ስለኛ - አውደ ርእይ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 21  ቀን  2004 ዓ.ም.)ባለፈው ሳምንት የጀመርነው የቆሻሻ ጉዳይ በይክረም አቆይተን ለዛሬ ወቅታዊ ጉዳይ እናነሳለን። የፎቶ አውደ ርእይ በብሔራዊ ሙዚየም - እስከ ሐምሌ 17 ቀን ድረስ ይቆያል። አውደ ርእዩ ስለዛፍ፤ ስለውኃ፤ ስለአፈር፤ ስለሕይወት ነው። በአጭሩ ስለኛ። የዘንድሮ ዓለም አቀፍ የአካባቢ ቀንን በማስመልከት በአካባቢ ጉዳዮችና በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ ንቃተ ህሊናን ከፍ ማድረግ እንደ ዓላማ ይዟል።

ቆሻሻን ከመጋራት ጽዳትን መጋራት


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 14  ቀን  2004 ዓ.ም.)በቅርቡ በከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትሩ የተመራና ከአዲስ አበባ መስተዳድር የሥራ ኃላፊዎችም አባል የሆኑበት የልኡካን ቡድን ወደ ሩዋንዳ ኪጋሊ አምርቶ ነበር። ኢቲቪ እንደዘገበው ሚኒስትሩ በኪጋሊ ከተማ ጽዳት ተገርመዋል - ‘ለውርርድ ያህል መንገድ ላይ የተጣለ ቆሻሻ አይታይም’ እስኪሉ ድረስ። ኢቲቪ ያሳየን የከተማዋ ጸዳ ያሉና አረንጓዴ አደባባዮች ምስልም ሚኒስትሩና ዘጋቢው በቃል የገ ልጹትን የሚደግፉ ነበሩ። በአላማው ውስጥ ‘ኪጋሊ እንዴት እንዲህ ጸዳች?’ ‘አዲስ አበባን እንዴት ብናደርጋት ነው ጸዳ ያለች ሆና የምትዘልቀው?’ የሚሉትን ጥያቄዎች መመለስን ያካተተው ተልእኮ ‘አሁን ገብቶናል!’  በሚል ድምዳሜ የተጠቃለለ ይመስላል - እንደ ኢቲቪ ዘገባ። ምን እንደገባቸው ወይም የሩዋንዳ አቻዎቻቸው ምን አይነት ጠንቋይ እየቀለቡ ኪጋሊን እንደዛ እንዳደርጓት ዘገባው አልነገረንም። በአጠቃላይ ከቅርብም ከሩቅም የልምድ ልውውጥ ማድረጉ ጥሩ ነው። አዲስ አበባ ግን ‘ኪጋሊ ድረስ ሳይኬድ መደረግ ያለበት ነገርም ነበር አለም!’ ትላለች - እነሆ እንስማት።

ስብሰባ ቅዳ ስብሰባ መልስ!


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 7  ቀን  2004 ዓ.ም.)  ባለፈው ቅዳሜ ከጠዋቱ አንድ ሰዓት አካባቢ አዲስ አበባ ስገባ በጭጋጋማውና እርጥበታማው ማለዳ ከቦይንጉ መውጫ በር ላይ ቆሜ ከከተማይቱ ገላ በቅጽበት መቃኘት የምችለውን ያህል በስስት ስቃኝ የሆነ በተስፋ የረሰረሰ ደስታ ተሰማኝ - ከማውቃት በላይ ከምጠብቃት በላይ አረንጓዴ የሆነች መሰለኝ። የታየኝ ለውጥ በክረምቱ ምክንያት የተፈጠረ? ወይስ የመውረጃ መማው የሰጠኝ የሸገር ከፊል ቁንጮ የተገደበ እይታ? ወይስ የምር አዲስ አበባችን ለመለመች?

ተግባቦት

(ጌታቸው አሰፋ፤ ሰኔ 23 ቀን  2004 ዓ.ም.)   ባደጉት አገሮች ያሉት የከተማ ነዋሪዎች በከተማቸው ውስጥ ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ለመንቀሳቀስ መኪና ባይኖር ይፈጅባቸው የነበረው ጊዜና በመኪና ሲጠቀሙ የሚፈጅባቸው ጊዜ ተቀራራቢ ሆኖ ነው የተገኘው - በአንዳንድ አገሮች የተደረጉ ጥናቶችን ስንመለከት። ለምን ቢባል በየመንገዱ ያለው በመኪና ብዛት የሚፈጠረው መጨናነቅና በየመብራቱ መቆም በመኪና መሄድ ሊያመጣው ይችልና ይገባ የነበረው በፍጥነት መድረስን ዋጋ ስላሳጣው ነው።

አረንጓዴ ኮከቦች




(ጌታቸው አሰፋ፤ ሰኔ 9 ቀን  2004 ዓ.ም.)   ኢትዮጵያ የሚሰሩትን የሚያውቁ አብሪዎች በየመስኩ ያስፈልጋታል ብለን ጀምረን ነበር ባለፈው እትም። የሚሰሩትን የሚያውቁ ማለት በመረጡት ጉዳይ ላይና ዙሪያ ከልብ በልብ ለመስራት ልባቸውን ከአእምሮአቸው ጋር አዋህደው የሚሰሩ ማለት ነው ብለን ነበር። እንደነዚህ አይነት አብሪዎች ውሎ አድሮ ቢያንስ አይን ላላቸውና ብርሃንን ለሚወዱ ሁሉ የሚያበሩ አብሪዎች ናቸው ብለን ከድርጅቶች ሁለት አንስተናል። በአካባቢና በኃይል ጉዳይ ዙሪያ ብዙ ናቸው ባይባሉም አረንጓዴ አብሪ ግለሰቦችም አሉ። የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ ከልማትና ከእድገት ጋር እንደሚጣረስ ተደርጎ በሚቀርብባቸው የእኛ አይነት አገሮች ውስጥ አረንጓዴ አብሪዎች እጅግ ውድ ናቸውና ለዛሬ ሁለት ግለሰቦችን በአረንጓዴ ኮከብነታቸው ብርሃናቸውን እዘክራለሁ።

አረንጓዴ አብሪዎች


(ጌታቸው አሰፋ፤ ግንቦት 25 ቀን  2004 ዓ.ም.)  አገራችን ኢትዮጵያ የሚሰሩትን የሚያውቁ አብሪዎች በየመስኩ ያስፈልጋታል። የሚሰሩትን የሚያውቁ በዚህ አገባብ የፈለገው ነገር ቢመጣ፤ ምንም እንቅፋት ቢመጣ፤ ሰው ቢሰማም ባይሰማም፤ በመረጡት ጉዳይ ላይና ዙሪያ ከልብ በልብ ለመስራት ልባቸውን ከአእምሮአቸው ጋር አዋህደው የሚሰሩ ተብሎ ይተርጎም። እንደነዚህ አይነት ሰዎች ወይም ድርጅቶች ውሎ አድሮ ቢያንስ አይን ላላቸውና ብርሃንን ለሚወዱ ሁሉ የሚያበሩ አብሪዎች ናቸው። በአካባቢና በኃይል ጉዳይ ዙሪያም ብዙ ናቸው ባይባሉም አረንጓዴ አብሪዎች አሉ። የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ የምር አቀንቃኞችን ከሞላ ጎደል እንደ በጎ ሚና ተጫዋችነት ማየት ቀላል ባልሆነባቸው የእኛ አይነት አገሮች ውስጥ እንደዚህ አይነት አረንጓዴ አብሪዎች ብርቅ ናቸው። ለዛሬ ሁለት ድርጅቶችን በአረንጓዴ አብሪነታቸው ብርሃናቸውን እንዘክራለን።

ደን-በላ ኩባንያዎችን ወዲያ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ግንቦት 11 ቀን  2004 ዓ.ም.) በአዲስ ጉዳይ መጽሔት በዚህ የአረንጓዴ ጉዳይ አምድ የበኩር ጽሑፌን ከጻፈኩ እነሆ አንድ ዓመት ከሦስት ወር አለፈኝ። የጽሑፉ ማጠንጠኛ ዛሬም የተመለስኩበት ርእስ የባዮዲዝል ነገር ሲሆን የተለያዩ ነጥቦች የተነሱበት ነበር። በአገራችን በቀጥታ ለሰው ምግብ ከማይውሉና ለባዮዲዝል ጥሬ እቃነት ይሆናሉ ከተባሉት ጥሬ እቃዎች መካከል በዋናነት ጃትሮፋንና ጉሎን እንዲሁም በተወሰነ ደረጃ የፓልም ዘይት እንደሚገኙበት አይተን ነበር። በወቅቱ በነበረው መረጃ ወደ ሰባ የሚጠጉ ባለሃብቶች ጃትሮፋን በማልማት ሥራ ላይ ለመሰማራት ፈቃድ ወስደዋል መባሉን፤ ከነዚሁ ወደ አሥራ አምስት የሚሆኑት ደግሞ ባለሀብቶች በደቡብ ኢትዮጵያ፤ በአማራ፤ በኦሮሚያ፤ በትግራይ፤ በቤንሻንጉል ጉሙዝና በሶማሌ ክልሎች ውስጥ በመሥራት ላይ እንደሚገኙ እንደተነገረ ወዘተ አንስተን ነበር።