Tuesday, January 22, 2013

ዋልያዎች ለዋልያዎች - ዘኳስ ለዘሜዳ

(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥር 11 ቀን  2005 ዓ.ም.) ለዛሬ ስለ ሁለት ዋልያዎች እንጽፋለን - የኢትዮጵያችን የብቻዋ ስለሆነ እንስሳው ዋልያና ዋልያ ተብሎ ስለሚጠራው ብሔራዊው የእግር ኳስ ቡድናችን። በተለይ ስለ ሁለተኛው ዋልያ ለመጻፍ ወይም መጻፍ ለመጀመር ዛሬ ምቹ ነው። ብሔራዊ ቡድናችን የያዘውን መጠሪያ ስም ያገኘው ከብርቅየው እንስሳ ‘ዋልያ አይቤክስ’ ስም ነው። የአሰያየም ሂደቱ በተመለከተ ዝርዝር መረጃ የለኝም (እነ ደጉ፤ አዳነና ጀማልም አናውቀውም ሲሉ ሰምቻለሁ)። ዋልያ አይቤክስ የኢትዮጵያ ከኢትዮጵያ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ሊሆን እንደሚችል ግን መገመት ይቻላል። ስለ ሁለቱም ዋልያዎች (ዋልያ ዘሜዳና ዋልያ ዘኳስ) በተራበ ተራ (አሁን ባይርበኝ ኖሮ ‘በተራ በተራ’ ብዬ እጽፈው ነበር) እናነሳና ከዛም መልሰን እናገናኛቸዋለን።

እነሱ ከእኛ ወይስ እኛ ከነሱ?

(ጌታቸው አሰፋ፤ ጥር 4 ቀን  2005 ዓ.ም.) በውጪው ዓለም ገና እና አዲስ ዓመት በስድስት ቀናት ልዩነት የሚከሰቱ ሁለት በዓላት ሲሆን መዘዛቸው ደግሞ እጅግ ከፍተኛ ነው። በምዕራቡ ዓለም የገና በዓል ከጊዜ ወደ ጊዜ ትርጉሙም ሚናውም እየተቀየረ መምጣቱን ማየት ይቻላል። እዚህ ካናዳ ውስጥ በአንድ ትምህርት ቤት ህጻናት ከቤተሰቦቻቸው ለተለያያ ትውልድ የገና በዓል የሚሰጠው ትርጉም ምን እንደነበር ጠይቀው እንዲጽፉ የቤት ስራ ይሰጣቸዋል። አንዱ ቅድመ አያቱን አያቱንና አባቱን ጠይቆ መጣ። ሴቷ ቅድመ አያቱ በዘመናቸው ጊዜ የነበረውንና የገና ብስኩት ላይ ስለሚቀባው ክሬም አንስተው ለዛን ዘመን ውድ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ለገና ብቻ ተቀብቶ ስለሚበሉት እንዴት በጉጉት ይጠብቁት እንደነበርና ያኔ የሰፈር ሰዎች አንድ ላይ ሆነው ያከብሩ እንደነበር አጫወቱት። አባታቸው ሚንስተር የነበሩት አያቱ ደግሞ የገና በዓል ለሳቸው ዘመን ሰዎች ጎዳና ተዳዳሪዎችን የመርጃ፤ ቤተ ክርስቲያን ሄደው ዝማሬ ማቅረቢያና ጎረቤታሞች ምግብና ደስታ የሚጋሩበት እርስ በርስ እየተደጋገፉ የሚያከብሩበት በዓል እንደነበር ነገሩት። አባቱን ሲጠይቅ ያገኘው መልስ ደግሞ የገና በዓል አከባበር ሌላ ቅርጽና ይዘት መምጣቱን ማየት የሚያስችል ነበር። አባትዬው ስለ አሻንጉሊቶችና ትልልቅ የፕላስቲክ መጫዎቻዎች እንደስጦታ መስጠት ዋነኛው የበዓሉ መገለጫ እየሆኑ መምጣታቸውንና ከዚህም ጋር በተያያዘ  ወላጆች ስጦታዎችን ለመግዛት አቅም በሚያጡበት ጊዜ እንዴት ጫናም ሀዘንም ይሰማቸው እንደነበር አጫወቱት።

Tuesday, January 8, 2013

ከጤንነት የሚሻል ሕክምና የለም

(ጌታቸው አሰፋ፤ ታኅሣሥ 20 ቀን  2005 ዓ.ም.)  ዛሬ የምጽፍበት ጉዳይ ከአረንጓዴ ጉዳይ ጋር ምን አገናኘው ለምትሉ አስቀድሜ መልስ ልስጥ። በአካባቢ ጥበቃም ሆነ በኃይል አቅርቦትና ፍጆታ ዙሪያ በአገሪቱ መዋዕለ ንዋይ ፈሶባቸው የሚሰሩ ስራዎች ወጪ ቆጣቢ ሆነው ውጤታማ እንዲሆኑ ካስፈለገ ከእውቀት አኳያ አንዱን ሳይጥል ሌላውን ሳያንጠለጥል መሆን አለበት። ከዚህ በላይ ደግሞ የማንኛውም አገር ልማታዊ ጉዞ በእውቀት ላይ መመስረት አለበት። በዚህ ሁሉም ሰው ከሞላ ጎደል ይስማማል። እውቀት ደግሞ ከመማር ይገኛል። በዚህም ብዙ ልዩነት አይኖርም። ጥያቄ የሚነሳው ግን ‘መማር ምን ማለት ነው?’ ‘ሰው የትና ከማን ይማራል?’ ‘ከየትና ከማንስ መማር አለበት?’ በሚሉት ዙሪያ ላይ ነው። በአገራችን በየእርከኑ መደበኛ ትምህርት ቤትና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ገብቶ የሚማረው ሰው ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ ይገኛል። ለፈጣንና አዛላቂ እድገት የተማረ ሰው ቁጥር መጨመሩ አስፈላጊ ነውና ደግ ነው።