Saturday, November 12, 2011

350 የካርበን ዳይኦክሳይድ ፊኛዎች?


(ጌታቸው አሰፋ)ይህ ካለፈው የቀጠለ በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ የሚያጠነጥነው ጽሑፍ ነው። ለዛሬ ስለ ሳይንስ በተቻለ መጠን ቀለል አድርገን እናወራለን። የአየር ንብረት ለውጥ ማለት በዓለም ደረጃና በረጅም ጊዜ የሚታዩ የለውጥ መገለጫ የሆኑት የከባቢ አየር ሙቀት፤ የዝናብ መጠንና የመሳሰሉት መገለጫዎች መለወጥ ማለት ነው። በአንድ ቦታና በአጭር ጊዜ ያለው የአየር ሁኔታ ለውጥ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ሊገናኝም ላይገናኝም ይችላል። 
የመስተዋታዊ ቤተ-ተክል ጠንቅ
የአየር ንብረት ለውጥ ሉላዊ ሞቅታ ተብሎም ይጠራል። ለውጡም የሚገለጸው በዓለም የከባቢ አየር አማካይ ሙቀት መጨመር ነው። በሌላ በኩል የመስተዋታዊ ቤተ-ተክል ጠንቅ ተብሎም ይታወቃል። ይህን ስም ያገኘው ግድግዳቸውና ጣራቸው ከመስተዋት ወይም ከፕላስቲክ ከሚሰሩት ለአትክልቶች ለአበቦችና ለመሳሰሉት ማልሚያ ከሚሆኑት ቤቶች ጋር በተያያዘ ነው።  በነዚህ ቤቶች የፀሐይ

Saturday, November 5, 2011

የአየር ንብረት ለውጥና ፍኖተ ደርባን


(ጌታቸው አሰፋ)የዛሬውና የቀጣዩ ጽሑፌ ትኩረት በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ ይሆናል። ምክንያት - አለም አቀፉ አስራ ሰባተኛው የአየር ንብረት ለውጥ ባለጉዳይ አካላት ጉባኤ ከፊታችን ህዳር 18 እስከ  ህዳር 29 በደቡብ አፍሪካ ደርባን ከተማ ስለሚካሄድ። 
ላለፉት አስራ አራት ዓመታት የተካሄዱት አለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ድርድሮች የሚያጠነጥኑት የኪዮቶ ፕሮቶኮል ተብሎ በሚጠራው ስምምነት ዙሪያ ነው። የኪዮቶ ፕሮቶኮል ባለ ሀያ ስምንት አንቀጽና ሁለት አባሪዎች ስምምነት ሲሆን ጃፓን በሚገኘው የኪዮቶ ከተማ ታህሳስ ሁለት 1990 .. የጸደቀ ነው።

Thursday, October 13, 2011

ባለአረንጓዴ ቀበቶ ጀግና


(ጌታቸው አሰፋ) ዛሬ ይህ አምድ ኬንያዊቷን ዋንጋሪ ማታይን ያስባል። ዋንጋሪ ሙታ ሜሪ ጆ ማታይ ከሰባ አንድ ዓመታት በፊት በሞኞች ቀን(April 1) የተወለዱ ልባም ሴት ነበሩ።  የመጀመሪያ ዲግሪያቸውንና ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በስነ-ህይወት ከአሜሪካ ዩኒቨርስቲዎች የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ደግሞ በእንስሳት ጤና ሳይንስ ስነ-ብልት ጥናት ከናይሮቢ ዩኒቨርስቲ አግኝተዋል። እሁድ መስከረም አስራ አራት 2004 ዓ.ም. በሞት ተለዩን። ሥራቸው ግን ከመንደራቸው፤ ከአገራቸውና ከአህጉራቸው አልፎ ከፍተኛ ዓለም አቀፋዊ እውቅናን ያገኘ ህያው ሥራ ሆኖ ይቀጥላል።  

ቀመሩ እንዲሰምር

(ጌታቸው አሰፋ)ስለ ግብርና እጽፋለሁ - ለዛሬ። መንግሥት ሁለት የማዳበሪያ ፋብሪካዎችን እገነባለሁ ማለቱ ነው መነሻዬ። መልካም ዜና ነው። እስቲ ወደ ኋላ ከመቶ ሃምሳ ዓመታት በላይ እንንደርደር።
ከአጼ ቴዎድሮስ ጋር ለአሥር ዓመታት በአገራችን የኖረ ስዊዘርላንዳዊው ሚሶንያዊ ቴዎፍሎስ ቫልድማየር በዚህ ወር ግን ከ153 ዓመታት በፊት ወደ አቢስኒያ ተጓዘ። ከአምስት ወር በኃላም ገባ። ይህ ከሆነ ከሀያ ስምንት ዓመታት በኋላም ስለአሥር ዓመት ቆይታው መጽሐፍ ጻፈ (የተሳሳቱ መረጃዎች ያሉበት)። በመጽሐፉ የዛሬው ጉዳዬ ስለሆነው እርሻችንና ተያያዥ ነገሮችን በተመለከተ የተጻፈውንና የተሳሳተ ነው የሚያስብል ነገር ያላገኘሁለትን ወደ አማርኛ እንዲህ መልሼዋለሁ። 

በዓል - ከጓዳ እስከ አካባቢ

(ጌታቸው አሰፋ) እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ። ከአንድ ሁለት ሳምንት በፊት የሸገር ራዲዮ “ዳጉ አዲስ”ን እያዳመጥኩ ነበር- በኢንተርኔት የቀጥታ ስርጭት። ወንዶች ሴቶችን በቤት ሥራ ማገዝ አለባቸው ወይስ የለባቸውም በሚል ርዕስ ስር ከተለያዩ ወጣቶች ጋር ቃል ምልልስ ያደርጋሉ - ዳጉዎች። ሁለት ወንድ ወጣቶች ቤታቸው ውስጥ ሽሮ ወጥ ሲሠሩ ከፕሮግራሙ አዘጋጆች አንዱ ተገኝቶ አሠራራቸውን በድምጽ ለራዲዮ አድማጮች ያስተላልፋል። ልጆቹና ጋዜጠኛው እያወሩ ከጀርባቸው አንድ አውራ ዶሮ ድምጹን ከፍ አድርጎ አሰምቶ ይጮሃል። የአሥር ወር ልጄን አየሁት። እየጮኸ ያለው አውራ ዶሮ መሆኑን ሊያውቅ እንደማይችል አሰብኩ። የእሱ አስተዳደግ በአካል ከሚታይ አውራ ዶሮ ጋር ያለው ርቀት የኔ አስተዳደግ ከአውራ ዶሮ ጋር ከነበረው ቁርኝት ጋር ያለው ልዩነት እያስደመመኝ ዓመት በዓል በመጣ ቁጥር ስለማስበው ነገር ማብሰልሰል ጀመርኩ - ስለ ዶሮ ወጥ።

Friday, September 2, 2011

የብክለት ወጥ


(ጌታቸው አሰፋ) አዲስ አበባ የመጀመሪያዋን መኪና ከዛሬ 104 ዓመት በፊት አስተናገደች - ታህሳስ 22 1889 ዓ.ም.። የታርጋ ቁጥሯ D3130 ነበር ተብሏል። አስር ሚልዮን ሕዝብ ያስተዳድሩ የነበሩት አጼ ምኒልክ ቴሌፎንን ወደ አገራችን ባስገቡ ከአራት ዓመት በኋላ ያስገቧት ነች። መጀመሪያ አለማማጃቸው፤ ከዛም እሳቸው፤ ከዛም ሾፌራቸው የነበረው ህንዳዊው ኤዳልጂ የነዷት መኪና ታወጣው የነበረ በካይ - ለምሳሌ ካርቦን-ዳይ-ኦክሳይድ - የአዲስ አበባን ንጹህ አየር በመቀላቀል አሃዱ ያለ አውቶሞቢላዊ በካይ ሆነ - የአገራችን የአካባቢ ብክለት ታሪክ ቅምሻ

Sunday, August 14, 2011

የምር አቀንቃኞች


(ጌታቸው አሰፋ) በወቅቱ እሠራበት የነበረው የባህርዳር ዩኒቨርስቲ ገና መጀመሩ ነበር - እንደ ዩኒቨርስቲ። ከመደበኛ ሥራዬ ውጪ የአካባቢና የተፈጥሮ ሀብት ጉዳይ የሚገደን ሰዎች ተሰባስበን ክልላዊ የአካባቢ ጥበቃ ጉዳዮች ላይ ግንዛቤ በማስጨበጥ ሥራዎች ላይ የሚያተኩር መንግሥታዊ ያልሆነ ማኅበር አቋቁመን መንቀሳቀስ ጀመርን።እኔ የማኅበሩ ጸሐፊ፤ በግብርና ቢሮ የሚሠራ ሌላ ባለሙያ ደግሞ ሰብሳቢ ሆነን ነበር።  በወቅቱ የባህርዳር ዩኒቨርስቲ ለበርካታ ዓመታት በፓሊቴክኒክነት የቆየውን ግቢ ወደ ቴክኖሎጂ ፋኩልቲ ደረጃ ለማሳደግ አስፈላጊ የነበሩ ግንባታዎችን በስፋት እያጧጧፈ ነበር። ግቢው ቀድመውኑም ቢሆን በጣም ሰፊ ነበርና የቦታ ጥበት አልነበረውም። ይሁንና እስካሁን ድረስ በማይገባኝ ምክንያት ነባር ዛፎች እየተቆረጡ  የነበሩበት ቦታ ላይ ህንጻዎች መተካት ጀመሩ። አንዳንዶቹ ዛፎች የማስፋፋቱ ሥራ ከመጀመሩ ከሠላሳ አራት ዓመታት በፊት ከተቋቋመው ፓሊቴክኒክ ግቢ በላይ እድሜ-ጠገብ ነበሩ።

Wednesday, July 27, 2011

የነፍስ ቁርጥማት


(ጌታቸው አሰፋ)ድርቅ አጥቢያዊ መነሻና ምክንያት አለው። አሁን አሁን ደግሞ እንደ ሉላዊ አባባሽ ምክንያትና መነሻ የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ(በካባቢ አየር ሙቀት መጨመር የሚገለጸው) ይጠቀሳል። ኢትዮጵያ ውስጥ ድርቅ መከሰት የጀመረው የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ሰውኛ መንስኤው ይበልጥ እየተረጋገጠ ከመምጣቱ ቢያንስ መቶ ዓመታት በፊት ነው። በመፍትሔ ደረጃ አጥቢያዊ መነሻው ላይ ስናተኩር የሚጨበጥ ነገር ማድረግ እንችላለን። ሉላዊ መነሻችን እንደ አገር ብቻችንን በተናጠል ከኃሌ-ኵሉ ሆነን የምንፈታው አይደለምና። በዛ ላይ አጥቢያዊ ምንጩን ስናደርቅ ሉላዊ ድርሻችንን ተወጣን ማለት ስለሚሆን አሪፍ ነው።
ለእውቀት ያህል ግን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ በአንዳንድ ቦታዎች ድርቅን ሲያባብስ  በሌሎች ቦታዎች ደግሞ የጎርፍ መጥለቅለቅን ያመጣል (ሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ)። 

Wednesday, July 13, 2011

“እቃሻሻ”

(ጌታቸው አሰፋ)(ደረቅ) ቆሻሻን የሆነ እቃ የቅርብ ዘመድ አድርገን ልንቆጥረው እንችላለን። ዝምድናው በተለያየ መልኩ ሊገለፅ የሚችል ነው። የእቃው አያቶች የሆኑትን ጥሬ ዕቃዎች ከማልማት ሂደት ጋር የሚገኝ ቆሻሻ አለ። እቃው ሲመረት የሚፈጠርም አለ። እቃው ጥቅም ላይ ሲውልም በማርጀት ወይም በመበላሸት ወይም ተጠቃሚው በሌላ ምክንያት እቃውን መጠቀም ሲያቆም የሚፈጠረውም ሌላው ነው።
የቆሻሻ መጥፎነት  - መጥፎ ከሆነ - ከመጠኑና ከይዘቱ ጋር የሚተሳሰር ነው። “ቆሻሻህን አሳየኝና ማንነትህን እነርግርሃለሁ” የሚል አባባል አለ ሲባል ከሰማን ኖረም አልኖረም አባባሉ ትክክል ስለሆነ የለም ብለን ባንከራከር ይሻላል።

Wednesday, June 29, 2011

የችጋርን ቀለበት ሰበራ


(ጌታቸው አሰፋ)ቀለበት የቱ ጋ እንደሚጀምር ለማወቅ ያስቸግራል። እንደ ቀለበት እንዲቀጥል የምንፈልገው በጎ ቀለበት ከሆነ የትስ ቢጀምር ምን ገዶን። መሰበር ያለበት ክፉ ቀለበት ከሆነ ግን የቱ ጋ ነው የጀመረው የሚለውን ጥያቄ መመለስ ወሳኝ ነው። የአገራችን አካባቢ ጉስቁልና እንዲያገግም ለማድረግ በየጊዜው የተለያዩ እርምጃዎች ተወስደዋል።  እየተወሰዱም ነው። ተፈላጊው ውጤት በምንመኘው ልክና ጥራት ግን ለማየት አልቻልንም - እስካሁን። የዚህ እንቆቆልሽ  ቁልፍና የችግራችን መፍትሔ የሚያያዘው የችግሩን ክፉ ቀለበትነት ከመገንዘብ ጋር ነው።  

Wednesday, June 15, 2011

የሚደላን ማመቻመች

(ጌታቸው አሰፋ) ለዛሬ ስለመሬት እጽፋለሁ። ኢትዮጵያችን እንደ አገር ምን ምን እንደሚያስፈልጋት የታወቀ ነው። በራሷ አቅም ህዝቧን መመገብ፤ የውጪ ምንዛሪ ምንጮችን ማስፋት፤ ለዜጎችዋ ቁጥረ-ብዙ የሥራ እድልን መፍጠር፤ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ለማበልጸግ የሚያስችሉ እድሎችን መፍጠርና መጠቀም አለባት። እነዚህን በአጥጋቢ መጠንና ጥራት ማድረግ ያለመቻልዋን የሚያሳብቁ ነባራዊ ተግዳሮቶችን ለመግጠም አገራዊና ዓለም አቀፋዊ ክስተቶች ግንዛቤ ውስጥ መግባት አለባቸው። በተለይ በዓለም ገበያ ላይ ጥገኛ ከመሆን አልፈን የዓለም ገበያን እኛ ላይ ይሄ ነው በሚባል ደረጃ ጥገኛ ለማድረግ ያልቻልን እኛና መሰል አገሮች ዓለም አቀፋዊ የለውጥ ዜማዎችን ተከትለን እስክስ ማለታችን የግድ ሆኗል።

Wednesday, June 1, 2011

ታሪከ-ቁስ


(ጌታቸው አሰፋ) ታሪክ ሠሪም ባለ ታሪክም ነው ሰው - በሰፊው እንደሚታመንበት። እያንዳንዱ እሴት-አዘል ቁስም (ምርትና አገልግሎት) የራሱ የሆነ ታሪክ አለው -  “ታሪከ ቁስ” ብንለውስ።  አጭር ወይም ረጅም ሊሆን ይችላል። ጥሩም መጥፎም ሊሆን ይችላል። 
የአንድ ምርት ወይም አገልግሎት ታሪክ ሲመረትና ጥቅም ላይ ሲውል የሚያልፍበትን ሂደት የሚያጠቃልል  በጥንተ-ተፈጥሮ  ምንጩ ጀምሮ በጥንተ-ተፈጥሮ ማረፊያው የሚያበቃ ሰንሰለታዊ  ዑደትን የሚያጠቃልል ነው።  ባለሁበት ዩኒቨርስቲ በዚህ ሰንሰለታዊ ዑደት ወቅት በአካባቢ አየር፤ ውኃና የብስ ላይ የሚያደርሰውን ተጽእኖ የማስላትና የመገምገም ዘይቤ ነው “ወንበር ዘርግቼ” ጥናትና ምርምር የማደርገውና ትምህርትም የምሰጠው።

Wednesday, May 18, 2011

መከላከያና አካባቢ

(ጌታቸው አሰፋ) ጠበብ አድርገን ካየነው ኦሳማ ቢን ላደንን የመግደል ተልእኮ የፈጸሙት 4 ሄሊኮፕቶሮች፤ 24 ወታደሮች (እንደ ቆጣሪው ቢለያይም) እና አንድ “ካይሮ” የተሰኘ ስልጡን ውሻ ናቸው። አስፍተን ካየነው ግን ቢን ላደንን አንዴ የተፈጥሮ አካባቢን ደጋግሞ እየገደለ ያለው ከአቦታባድ ተልእኮ በስተጀርባ ያለው በዘመናዊ ውስብስብ ቴክኖሎጂና በመደበኛ የስለላ አውታሮች የሚታገዘው ግዙፉ የአሜሪካ መከላከያ ነው። የአሜሪካ መከላከያ በዓለማችን ከፍተኛና ስርጭተ-ሰፊ አካባቢ በካይና አጎስቋይ ተቋም የመሆኑ ነገር ነው የዛሬ “የአረንጓዴ ጉዳይ” መቆያችን። 

Thursday, May 5, 2011

የ”ጉ” ቤት ለግብጾች


(ጌታቸው አሰፋ)ወደ ጀልባው የገባሁት ዘግይቼ ነበር። ያልተያዘ ወንበር ያለበት ጠረጴዛ ስፈልግ አንድ ብቻውን የተቀመጠ ሰው አየሁና ሄጄ ተቀላቀልኩ። ተዋወቅኩት። ይህ የሆነው የዛሬ ሰባት ዓመት ካናዳ ቶሮንቶ ነው። ከየአገሩ የተሰባሰብን የኮንፈረንስ ተሳታፊዎች ማብቂያ ላይ በኦንታሪዮ ሐይቅ እየተዟዟርን ለምንበላው እራት ነው ጀልባው ውስጥ የተገኘነው። “ከየት ነህ?” አልኩት። “ከዚሁ ከካናዳ ነኝ። ቶሮንቶ ዩኒቨርሲቲ ነው የማስተምረው” አለኝ። እኔም ተጠየቅኩ። “ከኢትዮጵያ ነኝ። አሁን ግን ስዊድን ነው ያለሁት” ብዬ የነበርኩበትን ዩኒቨርሲቲ ነገርኩት። ጠይምነቱ “መሠረትህ ግን ከየት ነው?” እንድለው ገፋፋኝ። ገና “ከግብጽ” ከማለቱ ሌላ ጥያቄ አስከተልኩ። “በጣም ጥሩ አጋጣሚ….. በመንግሥት ደረጃ ሳይሆን በተራ ግብጻዊ ደረጃ ስለአባይ የሚሰማችሁን ነገር እስቲ ንገረኝ።” የፊቱ  ቀለም ተቀያየረ።

ፉኩሺማዎች



(ጌታቸው አሰፋ)  በተወዳጅዋ ጃፓን በደረሰው አደጋ ወስዋሽነት ለዛሬ ስለኑክሌር ኃይል እጽፋለሁ። ሰኔ 27 1954 እ.አ.አ. የቀድሟ ሶቭየት ኅብረት መንግሥት  ንብረት የሆነው በዓለም የመጀመሪያው የኑክሌር ኃይል ማመንጫ  የኤሌክትሪክ ኃይል ማቅረብ ጀመረ። የኑክሌር ኃይል ማመንጫዎች ዋነኛ ግብአትና ጥሬ ዕቃ ዩራኒየም እንደሚሰኝ ይታወቅና እንቀጥል።  በዛው ዓመት ማለትም 1954 - አንድ ወር ቀደም ብሎ - ግንቦት 27  “ጄት” የተባለው የጥቁር አሜሪካዊያን መጽሔት እንደሚከተለው ዘገበ፡  “በዓለም ምርጥ ጥራት ካላቸው የዩራኒየም ማዕድናት ተርታ የሚሰለፍ በባለሥልጣናት ዘንድ ‘አብይ ግኝት’ የተባለለት  ዩራኒየም በኢትዮጵያ ተገኘ ሲሉ አጼ ኃይለ ሥላሴ በአዲስ አበባ ተናገሩ። አጼው የማዕድኑን መጠን ከመናገር  የተቆጠቡ ሲሆን ‘የባህር ኃይል መርከቦችን’ ጨምሮ ኢትዮጵያ ውስጥ ወታደራዊ ሰፈር ለማቋቋም የሚያስችል የ99 ዓመት ስምምነት ለማድረግ  ከአሜሪካ ባለስልጣናት ጋር እየተነጋገርን ነው ብለዋል።” 
ዛሬ በዓለም ወደ 31 በሚሆኑ አገሮች ውስጥ ወደ 480 የኑክሌር ማብላሊያዎች (ሳሳጥረው ማብልያዎች) ይገኛሉ - የዛሬ ወር በርዕደ መሬትና በውኃ ነውጥ አደጋ የደረሰበት የጃፓኖቹን 6 የፉኩሺማ ዳይቺ የኑክሌር ማብልያዎችን ጨምሮ ። 

Saturday, April 9, 2011

የነዳጅ አረቄ(ethanol) ድብልቅ


(ጌታቸው አሰፋ)በቅርቡ ለወራት ሳይከለስ የቆየው የተለያዩ የነዳጅ ዘይት ውጤቶች የችርቻሮ ዋጋ ተከልሷል። የቤንዚንና የነዳጅ አረቄ (ethanol) ድብልቅ በሊትር 16 ብር ከ55 ሳንቲም  ወደ 18 ከ33 ሳንቲም ከፍ እንዲል ከተደረገ በኋላ ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ወደ 17.88 ዝቅ እንዲል ተደርጓል። በመቀነስ የሂሳብ ስሌት ሲታይ— የ1ብር ከ33 ሳንቲም ጭማሪ አሳይቷል ማለት ነው። ምክንያት— የዓለም የድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ዋጋ መጨመር። የዓለም የድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ዋጋ መጨመሩ ምክንያት ደግሞ— የሰሜን አፍሪካና የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ውስጥ ላለፉት ሁለት ወራት የታየው አለመረጋጋት።

Friday, March 25, 2011

አዲስ አበባንና ባህር ዛፍን ያስገኘልን መዘዝና አንድምታው

(ጌታቸው አሰፋ) ጊዜው 1981 ዓ।ም। ነበር ። እኔም 11ኛ ክፍል ነበርኩ። መኝታ ቤታችን ውስጥ ከነበረው ቁም ሳጥን ላይ የእጅ መዳፍ የምታህል ላስቲካማ ወረቀት ተለጥፋለች። ውሃ ሰማያዊ መደብ፤ ቀይ ጠርዝ መሐል ላይ ቢጫ አበባ። ቁም ሳጥኑ ላይ ከተለጠፈች ሁለት ዓመት ሆኗታል። የአዲስ አበባን መቶኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀች ነበረች። በ1979 ዓ।ም। መሆኑ ነው። ዛሬ አዲስ አበባ የ124 ዓመት “ጎልማሳ” ነች። የአክሱም፤የጎንደር፤የላሊበላ፤የአንኮበር፤ የእድሜ የታናሽ ታናሽ - አዲስ አበባ። ከአዲስ አበባ መቆርቆር ጀርባ የነበረው መነሻ በጎ የሚባል አይነት አልነበረም። የማገዶ እና የቤት መሥርያ እንጨት እጥረት ጋር የተያያዘ መዘዝ ነው አዲስ አበባን ያስገኘልን።

ለብዙ የጥንት ስልጣኔዎች መንገራገጭ ምክንያት የሆነ መዘዝ። ለአንዳንድ ከተሞች መቆርቆዝ ለሌሎች ደግሞ መቆርቆር ምክንያት ሆኗል። በመቶዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት በቻይና በጃፓን የደን መጨፍጨፍና መመናመን ሰዎች የሚኖሩባቸውን ቦታዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲቀያይሩ አድርጓል።

Tuesday, March 15, 2011

እስካሁን ከመሬት በታች ያላገኘነውን ከመሬት በላይ ለማግኘት - በእንተ ባዮ ዲዝል

(ጌታቸው አሰፋ )ባዮ ዲዝል እንደ መደበኛው ዲዝል ከድፍድፍ ነዳጅ ዘይት የሚገኝ ሳይሆን ከእጽዋትና ከእንስሳት ተዋጽኦ (ዘይትና ሞራ) የሚመረት የዲዝል አይነት ነው። ለባለ ዲዝል ሞተር መኪኖችና ለዲዝል ጀነሬተሮች እንዲሁም ለመሳሰሉት የመገልገያ እቃዎች ይውላል።
አገራችን በ2003 ዓ.ም. የበጀት ዓመት በአጠቃላይ የነዳጅ ዘይት ውጤቶችን ከውጪ ወደ አገር ቤት ለማስገባት 23.60 ቢልዮን ብር ያስፈልጋታል። ይህም ዲዝልን ጨምሮ ከ2.2 ሚልዮን ቶን በላይ ነዳጅን ለማስገባት የሚውል ነው።ይህም ወጪ ከአጠቃላይ የአገሪቱ የዘንድሮ 72.2 ቢልዮን በጀት ወደ 32 ፐርሰንት የሚሆነውን ይሸፍናል።
ከውጪ የሚገባው ማንኛውም ምርት በአገር ውስጥ ምርት መተካት በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባሉና የባሕር በር በሌላቸው አገሮች ጠቀሜታው እጅግ የጎላ ነው። ይልቁንም በየቀኑ ከሚጨምረው የዓለም ነዳጅ ዋጋ አንጻር የነዳጅ ዘይትን በአገር ቤት ምርት መተካት መቻል ለአገራችን የሚኖረው አዎንታዊ አንድምታ በርካታ ነው።