Wednesday, June 1, 2011

ታሪከ-ቁስ


(ጌታቸው አሰፋ) ታሪክ ሠሪም ባለ ታሪክም ነው ሰው - በሰፊው እንደሚታመንበት። እያንዳንዱ እሴት-አዘል ቁስም (ምርትና አገልግሎት) የራሱ የሆነ ታሪክ አለው -  “ታሪከ ቁስ” ብንለውስ።  አጭር ወይም ረጅም ሊሆን ይችላል። ጥሩም መጥፎም ሊሆን ይችላል። 
የአንድ ምርት ወይም አገልግሎት ታሪክ ሲመረትና ጥቅም ላይ ሲውል የሚያልፍበትን ሂደት የሚያጠቃልል  በጥንተ-ተፈጥሮ  ምንጩ ጀምሮ በጥንተ-ተፈጥሮ ማረፊያው የሚያበቃ ሰንሰለታዊ  ዑደትን የሚያጠቃልል ነው።  ባለሁበት ዩኒቨርስቲ በዚህ ሰንሰለታዊ ዑደት ወቅት በአካባቢ አየር፤ ውኃና የብስ ላይ የሚያደርሰውን ተጽእኖ የማስላትና የመገምገም ዘይቤ ነው “ወንበር ዘርግቼ” ጥናትና ምርምር የማደርገውና ትምህርትም የምሰጠው።

Wednesday, May 18, 2011

መከላከያና አካባቢ

(ጌታቸው አሰፋ) ጠበብ አድርገን ካየነው ኦሳማ ቢን ላደንን የመግደል ተልእኮ የፈጸሙት 4 ሄሊኮፕቶሮች፤ 24 ወታደሮች (እንደ ቆጣሪው ቢለያይም) እና አንድ “ካይሮ” የተሰኘ ስልጡን ውሻ ናቸው። አስፍተን ካየነው ግን ቢን ላደንን አንዴ የተፈጥሮ አካባቢን ደጋግሞ እየገደለ ያለው ከአቦታባድ ተልእኮ በስተጀርባ ያለው በዘመናዊ ውስብስብ ቴክኖሎጂና በመደበኛ የስለላ አውታሮች የሚታገዘው ግዙፉ የአሜሪካ መከላከያ ነው። የአሜሪካ መከላከያ በዓለማችን ከፍተኛና ስርጭተ-ሰፊ አካባቢ በካይና አጎስቋይ ተቋም የመሆኑ ነገር ነው የዛሬ “የአረንጓዴ ጉዳይ” መቆያችን። 

Thursday, May 5, 2011

የ”ጉ” ቤት ለግብጾች


(ጌታቸው አሰፋ)ወደ ጀልባው የገባሁት ዘግይቼ ነበር። ያልተያዘ ወንበር ያለበት ጠረጴዛ ስፈልግ አንድ ብቻውን የተቀመጠ ሰው አየሁና ሄጄ ተቀላቀልኩ። ተዋወቅኩት። ይህ የሆነው የዛሬ ሰባት ዓመት ካናዳ ቶሮንቶ ነው። ከየአገሩ የተሰባሰብን የኮንፈረንስ ተሳታፊዎች ማብቂያ ላይ በኦንታሪዮ ሐይቅ እየተዟዟርን ለምንበላው እራት ነው ጀልባው ውስጥ የተገኘነው። “ከየት ነህ?” አልኩት። “ከዚሁ ከካናዳ ነኝ። ቶሮንቶ ዩኒቨርሲቲ ነው የማስተምረው” አለኝ። እኔም ተጠየቅኩ። “ከኢትዮጵያ ነኝ። አሁን ግን ስዊድን ነው ያለሁት” ብዬ የነበርኩበትን ዩኒቨርሲቲ ነገርኩት። ጠይምነቱ “መሠረትህ ግን ከየት ነው?” እንድለው ገፋፋኝ። ገና “ከግብጽ” ከማለቱ ሌላ ጥያቄ አስከተልኩ። “በጣም ጥሩ አጋጣሚ….. በመንግሥት ደረጃ ሳይሆን በተራ ግብጻዊ ደረጃ ስለአባይ የሚሰማችሁን ነገር እስቲ ንገረኝ።” የፊቱ  ቀለም ተቀያየረ።

ፉኩሺማዎች



(ጌታቸው አሰፋ)  በተወዳጅዋ ጃፓን በደረሰው አደጋ ወስዋሽነት ለዛሬ ስለኑክሌር ኃይል እጽፋለሁ። ሰኔ 27 1954 እ.አ.አ. የቀድሟ ሶቭየት ኅብረት መንግሥት  ንብረት የሆነው በዓለም የመጀመሪያው የኑክሌር ኃይል ማመንጫ  የኤሌክትሪክ ኃይል ማቅረብ ጀመረ። የኑክሌር ኃይል ማመንጫዎች ዋነኛ ግብአትና ጥሬ ዕቃ ዩራኒየም እንደሚሰኝ ይታወቅና እንቀጥል።  በዛው ዓመት ማለትም 1954 - አንድ ወር ቀደም ብሎ - ግንቦት 27  “ጄት” የተባለው የጥቁር አሜሪካዊያን መጽሔት እንደሚከተለው ዘገበ፡  “በዓለም ምርጥ ጥራት ካላቸው የዩራኒየም ማዕድናት ተርታ የሚሰለፍ በባለሥልጣናት ዘንድ ‘አብይ ግኝት’ የተባለለት  ዩራኒየም በኢትዮጵያ ተገኘ ሲሉ አጼ ኃይለ ሥላሴ በአዲስ አበባ ተናገሩ። አጼው የማዕድኑን መጠን ከመናገር  የተቆጠቡ ሲሆን ‘የባህር ኃይል መርከቦችን’ ጨምሮ ኢትዮጵያ ውስጥ ወታደራዊ ሰፈር ለማቋቋም የሚያስችል የ99 ዓመት ስምምነት ለማድረግ  ከአሜሪካ ባለስልጣናት ጋር እየተነጋገርን ነው ብለዋል።” 
ዛሬ በዓለም ወደ 31 በሚሆኑ አገሮች ውስጥ ወደ 480 የኑክሌር ማብላሊያዎች (ሳሳጥረው ማብልያዎች) ይገኛሉ - የዛሬ ወር በርዕደ መሬትና በውኃ ነውጥ አደጋ የደረሰበት የጃፓኖቹን 6 የፉኩሺማ ዳይቺ የኑክሌር ማብልያዎችን ጨምሮ ። 

Saturday, April 9, 2011

የነዳጅ አረቄ(ethanol) ድብልቅ


(ጌታቸው አሰፋ)በቅርቡ ለወራት ሳይከለስ የቆየው የተለያዩ የነዳጅ ዘይት ውጤቶች የችርቻሮ ዋጋ ተከልሷል። የቤንዚንና የነዳጅ አረቄ (ethanol) ድብልቅ በሊትር 16 ብር ከ55 ሳንቲም  ወደ 18 ከ33 ሳንቲም ከፍ እንዲል ከተደረገ በኋላ ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ወደ 17.88 ዝቅ እንዲል ተደርጓል። በመቀነስ የሂሳብ ስሌት ሲታይ— የ1ብር ከ33 ሳንቲም ጭማሪ አሳይቷል ማለት ነው። ምክንያት— የዓለም የድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ዋጋ መጨመር። የዓለም የድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ዋጋ መጨመሩ ምክንያት ደግሞ— የሰሜን አፍሪካና የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ውስጥ ላለፉት ሁለት ወራት የታየው አለመረጋጋት።

Friday, March 25, 2011

አዲስ አበባንና ባህር ዛፍን ያስገኘልን መዘዝና አንድምታው

(ጌታቸው አሰፋ) ጊዜው 1981 ዓ।ም। ነበር ። እኔም 11ኛ ክፍል ነበርኩ። መኝታ ቤታችን ውስጥ ከነበረው ቁም ሳጥን ላይ የእጅ መዳፍ የምታህል ላስቲካማ ወረቀት ተለጥፋለች። ውሃ ሰማያዊ መደብ፤ ቀይ ጠርዝ መሐል ላይ ቢጫ አበባ። ቁም ሳጥኑ ላይ ከተለጠፈች ሁለት ዓመት ሆኗታል። የአዲስ አበባን መቶኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀች ነበረች። በ1979 ዓ।ም। መሆኑ ነው። ዛሬ አዲስ አበባ የ124 ዓመት “ጎልማሳ” ነች። የአክሱም፤የጎንደር፤የላሊበላ፤የአንኮበር፤ የእድሜ የታናሽ ታናሽ - አዲስ አበባ። ከአዲስ አበባ መቆርቆር ጀርባ የነበረው መነሻ በጎ የሚባል አይነት አልነበረም። የማገዶ እና የቤት መሥርያ እንጨት እጥረት ጋር የተያያዘ መዘዝ ነው አዲስ አበባን ያስገኘልን።

ለብዙ የጥንት ስልጣኔዎች መንገራገጭ ምክንያት የሆነ መዘዝ። ለአንዳንድ ከተሞች መቆርቆዝ ለሌሎች ደግሞ መቆርቆር ምክንያት ሆኗል። በመቶዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት በቻይና በጃፓን የደን መጨፍጨፍና መመናመን ሰዎች የሚኖሩባቸውን ቦታዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲቀያይሩ አድርጓል።

Tuesday, March 15, 2011

እስካሁን ከመሬት በታች ያላገኘነውን ከመሬት በላይ ለማግኘት - በእንተ ባዮ ዲዝል

(ጌታቸው አሰፋ )ባዮ ዲዝል እንደ መደበኛው ዲዝል ከድፍድፍ ነዳጅ ዘይት የሚገኝ ሳይሆን ከእጽዋትና ከእንስሳት ተዋጽኦ (ዘይትና ሞራ) የሚመረት የዲዝል አይነት ነው። ለባለ ዲዝል ሞተር መኪኖችና ለዲዝል ጀነሬተሮች እንዲሁም ለመሳሰሉት የመገልገያ እቃዎች ይውላል።
አገራችን በ2003 ዓ.ም. የበጀት ዓመት በአጠቃላይ የነዳጅ ዘይት ውጤቶችን ከውጪ ወደ አገር ቤት ለማስገባት 23.60 ቢልዮን ብር ያስፈልጋታል። ይህም ዲዝልን ጨምሮ ከ2.2 ሚልዮን ቶን በላይ ነዳጅን ለማስገባት የሚውል ነው።ይህም ወጪ ከአጠቃላይ የአገሪቱ የዘንድሮ 72.2 ቢልዮን በጀት ወደ 32 ፐርሰንት የሚሆነውን ይሸፍናል።
ከውጪ የሚገባው ማንኛውም ምርት በአገር ውስጥ ምርት መተካት በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባሉና የባሕር በር በሌላቸው አገሮች ጠቀሜታው እጅግ የጎላ ነው። ይልቁንም በየቀኑ ከሚጨምረው የዓለም ነዳጅ ዋጋ አንጻር የነዳጅ ዘይትን በአገር ቤት ምርት መተካት መቻል ለአገራችን የሚኖረው አዎንታዊ አንድምታ በርካታ ነው።