Sunday, November 25, 2012

ስለኛ - አውደ ርእይ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 21  ቀን  2004 ዓ.ም.)ባለፈው ሳምንት የጀመርነው የቆሻሻ ጉዳይ በይክረም አቆይተን ለዛሬ ወቅታዊ ጉዳይ እናነሳለን። የፎቶ አውደ ርእይ በብሔራዊ ሙዚየም - እስከ ሐምሌ 17 ቀን ድረስ ይቆያል። አውደ ርእዩ ስለዛፍ፤ ስለውኃ፤ ስለአፈር፤ ስለሕይወት ነው። በአጭሩ ስለኛ። የዘንድሮ ዓለም አቀፍ የአካባቢ ቀንን በማስመልከት በአካባቢ ጉዳዮችና በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ ንቃተ ህሊናን ከፍ ማድረግ እንደ ዓላማ ይዟል።

ቆሻሻን ከመጋራት ጽዳትን መጋራት


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 14  ቀን  2004 ዓ.ም.)በቅርቡ በከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትሩ የተመራና ከአዲስ አበባ መስተዳድር የሥራ ኃላፊዎችም አባል የሆኑበት የልኡካን ቡድን ወደ ሩዋንዳ ኪጋሊ አምርቶ ነበር። ኢቲቪ እንደዘገበው ሚኒስትሩ በኪጋሊ ከተማ ጽዳት ተገርመዋል - ‘ለውርርድ ያህል መንገድ ላይ የተጣለ ቆሻሻ አይታይም’ እስኪሉ ድረስ። ኢቲቪ ያሳየን የከተማዋ ጸዳ ያሉና አረንጓዴ አደባባዮች ምስልም ሚኒስትሩና ዘጋቢው በቃል የገ ልጹትን የሚደግፉ ነበሩ። በአላማው ውስጥ ‘ኪጋሊ እንዴት እንዲህ ጸዳች?’ ‘አዲስ አበባን እንዴት ብናደርጋት ነው ጸዳ ያለች ሆና የምትዘልቀው?’ የሚሉትን ጥያቄዎች መመለስን ያካተተው ተልእኮ ‘አሁን ገብቶናል!’  በሚል ድምዳሜ የተጠቃለለ ይመስላል - እንደ ኢቲቪ ዘገባ። ምን እንደገባቸው ወይም የሩዋንዳ አቻዎቻቸው ምን አይነት ጠንቋይ እየቀለቡ ኪጋሊን እንደዛ እንዳደርጓት ዘገባው አልነገረንም። በአጠቃላይ ከቅርብም ከሩቅም የልምድ ልውውጥ ማድረጉ ጥሩ ነው። አዲስ አበባ ግን ‘ኪጋሊ ድረስ ሳይኬድ መደረግ ያለበት ነገርም ነበር አለም!’ ትላለች - እነሆ እንስማት።

ስብሰባ ቅዳ ስብሰባ መልስ!


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 7  ቀን  2004 ዓ.ም.)  ባለፈው ቅዳሜ ከጠዋቱ አንድ ሰዓት አካባቢ አዲስ አበባ ስገባ በጭጋጋማውና እርጥበታማው ማለዳ ከቦይንጉ መውጫ በር ላይ ቆሜ ከከተማይቱ ገላ በቅጽበት መቃኘት የምችለውን ያህል በስስት ስቃኝ የሆነ በተስፋ የረሰረሰ ደስታ ተሰማኝ - ከማውቃት በላይ ከምጠብቃት በላይ አረንጓዴ የሆነች መሰለኝ። የታየኝ ለውጥ በክረምቱ ምክንያት የተፈጠረ? ወይስ የመውረጃ መማው የሰጠኝ የሸገር ከፊል ቁንጮ የተገደበ እይታ? ወይስ የምር አዲስ አበባችን ለመለመች?

ተግባቦት

(ጌታቸው አሰፋ፤ ሰኔ 23 ቀን  2004 ዓ.ም.)   ባደጉት አገሮች ያሉት የከተማ ነዋሪዎች በከተማቸው ውስጥ ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ለመንቀሳቀስ መኪና ባይኖር ይፈጅባቸው የነበረው ጊዜና በመኪና ሲጠቀሙ የሚፈጅባቸው ጊዜ ተቀራራቢ ሆኖ ነው የተገኘው - በአንዳንድ አገሮች የተደረጉ ጥናቶችን ስንመለከት። ለምን ቢባል በየመንገዱ ያለው በመኪና ብዛት የሚፈጠረው መጨናነቅና በየመብራቱ መቆም በመኪና መሄድ ሊያመጣው ይችልና ይገባ የነበረው በፍጥነት መድረስን ዋጋ ስላሳጣው ነው።

አረንጓዴ ኮከቦች




(ጌታቸው አሰፋ፤ ሰኔ 9 ቀን  2004 ዓ.ም.)   ኢትዮጵያ የሚሰሩትን የሚያውቁ አብሪዎች በየመስኩ ያስፈልጋታል ብለን ጀምረን ነበር ባለፈው እትም። የሚሰሩትን የሚያውቁ ማለት በመረጡት ጉዳይ ላይና ዙሪያ ከልብ በልብ ለመስራት ልባቸውን ከአእምሮአቸው ጋር አዋህደው የሚሰሩ ማለት ነው ብለን ነበር። እንደነዚህ አይነት አብሪዎች ውሎ አድሮ ቢያንስ አይን ላላቸውና ብርሃንን ለሚወዱ ሁሉ የሚያበሩ አብሪዎች ናቸው ብለን ከድርጅቶች ሁለት አንስተናል። በአካባቢና በኃይል ጉዳይ ዙሪያ ብዙ ናቸው ባይባሉም አረንጓዴ አብሪ ግለሰቦችም አሉ። የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ ከልማትና ከእድገት ጋር እንደሚጣረስ ተደርጎ በሚቀርብባቸው የእኛ አይነት አገሮች ውስጥ አረንጓዴ አብሪዎች እጅግ ውድ ናቸውና ለዛሬ ሁለት ግለሰቦችን በአረንጓዴ ኮከብነታቸው ብርሃናቸውን እዘክራለሁ።

አረንጓዴ አብሪዎች


(ጌታቸው አሰፋ፤ ግንቦት 25 ቀን  2004 ዓ.ም.)  አገራችን ኢትዮጵያ የሚሰሩትን የሚያውቁ አብሪዎች በየመስኩ ያስፈልጋታል። የሚሰሩትን የሚያውቁ በዚህ አገባብ የፈለገው ነገር ቢመጣ፤ ምንም እንቅፋት ቢመጣ፤ ሰው ቢሰማም ባይሰማም፤ በመረጡት ጉዳይ ላይና ዙሪያ ከልብ በልብ ለመስራት ልባቸውን ከአእምሮአቸው ጋር አዋህደው የሚሰሩ ተብሎ ይተርጎም። እንደነዚህ አይነት ሰዎች ወይም ድርጅቶች ውሎ አድሮ ቢያንስ አይን ላላቸውና ብርሃንን ለሚወዱ ሁሉ የሚያበሩ አብሪዎች ናቸው። በአካባቢና በኃይል ጉዳይ ዙሪያም ብዙ ናቸው ባይባሉም አረንጓዴ አብሪዎች አሉ። የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ የምር አቀንቃኞችን ከሞላ ጎደል እንደ በጎ ሚና ተጫዋችነት ማየት ቀላል ባልሆነባቸው የእኛ አይነት አገሮች ውስጥ እንደዚህ አይነት አረንጓዴ አብሪዎች ብርቅ ናቸው። ለዛሬ ሁለት ድርጅቶችን በአረንጓዴ አብሪነታቸው ብርሃናቸውን እንዘክራለን።

ደን-በላ ኩባንያዎችን ወዲያ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ግንቦት 11 ቀን  2004 ዓ.ም.) በአዲስ ጉዳይ መጽሔት በዚህ የአረንጓዴ ጉዳይ አምድ የበኩር ጽሑፌን ከጻፈኩ እነሆ አንድ ዓመት ከሦስት ወር አለፈኝ። የጽሑፉ ማጠንጠኛ ዛሬም የተመለስኩበት ርእስ የባዮዲዝል ነገር ሲሆን የተለያዩ ነጥቦች የተነሱበት ነበር። በአገራችን በቀጥታ ለሰው ምግብ ከማይውሉና ለባዮዲዝል ጥሬ እቃነት ይሆናሉ ከተባሉት ጥሬ እቃዎች መካከል በዋናነት ጃትሮፋንና ጉሎን እንዲሁም በተወሰነ ደረጃ የፓልም ዘይት እንደሚገኙበት አይተን ነበር። በወቅቱ በነበረው መረጃ ወደ ሰባ የሚጠጉ ባለሃብቶች ጃትሮፋን በማልማት ሥራ ላይ ለመሰማራት ፈቃድ ወስደዋል መባሉን፤ ከነዚሁ ወደ አሥራ አምስት የሚሆኑት ደግሞ ባለሀብቶች በደቡብ ኢትዮጵያ፤ በአማራ፤ በኦሮሚያ፤ በትግራይ፤ በቤንሻንጉል ጉሙዝና በሶማሌ ክልሎች ውስጥ በመሥራት ላይ እንደሚገኙ እንደተነገረ ወዘተ አንስተን ነበር።