Friday, March 25, 2011

አዲስ አበባንና ባህር ዛፍን ያስገኘልን መዘዝና አንድምታው

(ጌታቸው አሰፋ) ጊዜው 1981 ዓ।ም। ነበር ። እኔም 11ኛ ክፍል ነበርኩ። መኝታ ቤታችን ውስጥ ከነበረው ቁም ሳጥን ላይ የእጅ መዳፍ የምታህል ላስቲካማ ወረቀት ተለጥፋለች። ውሃ ሰማያዊ መደብ፤ ቀይ ጠርዝ መሐል ላይ ቢጫ አበባ። ቁም ሳጥኑ ላይ ከተለጠፈች ሁለት ዓመት ሆኗታል። የአዲስ አበባን መቶኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀች ነበረች። በ1979 ዓ।ም। መሆኑ ነው። ዛሬ አዲስ አበባ የ124 ዓመት “ጎልማሳ” ነች። የአክሱም፤የጎንደር፤የላሊበላ፤የአንኮበር፤ የእድሜ የታናሽ ታናሽ - አዲስ አበባ። ከአዲስ አበባ መቆርቆር ጀርባ የነበረው መነሻ በጎ የሚባል አይነት አልነበረም። የማገዶ እና የቤት መሥርያ እንጨት እጥረት ጋር የተያያዘ መዘዝ ነው አዲስ አበባን ያስገኘልን።

ለብዙ የጥንት ስልጣኔዎች መንገራገጭ ምክንያት የሆነ መዘዝ። ለአንዳንድ ከተሞች መቆርቆዝ ለሌሎች ደግሞ መቆርቆር ምክንያት ሆኗል። በመቶዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት በቻይና በጃፓን የደን መጨፍጨፍና መመናመን ሰዎች የሚኖሩባቸውን ቦታዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲቀያይሩ አድርጓል።

Tuesday, March 15, 2011

እስካሁን ከመሬት በታች ያላገኘነውን ከመሬት በላይ ለማግኘት - በእንተ ባዮ ዲዝል

(ጌታቸው አሰፋ )ባዮ ዲዝል እንደ መደበኛው ዲዝል ከድፍድፍ ነዳጅ ዘይት የሚገኝ ሳይሆን ከእጽዋትና ከእንስሳት ተዋጽኦ (ዘይትና ሞራ) የሚመረት የዲዝል አይነት ነው። ለባለ ዲዝል ሞተር መኪኖችና ለዲዝል ጀነሬተሮች እንዲሁም ለመሳሰሉት የመገልገያ እቃዎች ይውላል።
አገራችን በ2003 ዓ.ም. የበጀት ዓመት በአጠቃላይ የነዳጅ ዘይት ውጤቶችን ከውጪ ወደ አገር ቤት ለማስገባት 23.60 ቢልዮን ብር ያስፈልጋታል። ይህም ዲዝልን ጨምሮ ከ2.2 ሚልዮን ቶን በላይ ነዳጅን ለማስገባት የሚውል ነው።ይህም ወጪ ከአጠቃላይ የአገሪቱ የዘንድሮ 72.2 ቢልዮን በጀት ወደ 32 ፐርሰንት የሚሆነውን ይሸፍናል።
ከውጪ የሚገባው ማንኛውም ምርት በአገር ውስጥ ምርት መተካት በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባሉና የባሕር በር በሌላቸው አገሮች ጠቀሜታው እጅግ የጎላ ነው። ይልቁንም በየቀኑ ከሚጨምረው የዓለም ነዳጅ ዋጋ አንጻር የነዳጅ ዘይትን በአገር ቤት ምርት መተካት መቻል ለአገራችን የሚኖረው አዎንታዊ አንድምታ በርካታ ነው።