Thursday, October 13, 2011

በዓል - ከጓዳ እስከ አካባቢ

(ጌታቸው አሰፋ) እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ። ከአንድ ሁለት ሳምንት በፊት የሸገር ራዲዮ “ዳጉ አዲስ”ን እያዳመጥኩ ነበር- በኢንተርኔት የቀጥታ ስርጭት። ወንዶች ሴቶችን በቤት ሥራ ማገዝ አለባቸው ወይስ የለባቸውም በሚል ርዕስ ስር ከተለያዩ ወጣቶች ጋር ቃል ምልልስ ያደርጋሉ - ዳጉዎች። ሁለት ወንድ ወጣቶች ቤታቸው ውስጥ ሽሮ ወጥ ሲሠሩ ከፕሮግራሙ አዘጋጆች አንዱ ተገኝቶ አሠራራቸውን በድምጽ ለራዲዮ አድማጮች ያስተላልፋል። ልጆቹና ጋዜጠኛው እያወሩ ከጀርባቸው አንድ አውራ ዶሮ ድምጹን ከፍ አድርጎ አሰምቶ ይጮሃል። የአሥር ወር ልጄን አየሁት። እየጮኸ ያለው አውራ ዶሮ መሆኑን ሊያውቅ እንደማይችል አሰብኩ። የእሱ አስተዳደግ በአካል ከሚታይ አውራ ዶሮ ጋር ያለው ርቀት የኔ አስተዳደግ ከአውራ ዶሮ ጋር ከነበረው ቁርኝት ጋር ያለው ልዩነት እያስደመመኝ ዓመት በዓል በመጣ ቁጥር ስለማስበው ነገር ማብሰልሰል ጀመርኩ - ስለ ዶሮ ወጥ።

Friday, September 2, 2011

የብክለት ወጥ


(ጌታቸው አሰፋ) አዲስ አበባ የመጀመሪያዋን መኪና ከዛሬ 104 ዓመት በፊት አስተናገደች - ታህሳስ 22 1889 ዓ.ም.። የታርጋ ቁጥሯ D3130 ነበር ተብሏል። አስር ሚልዮን ሕዝብ ያስተዳድሩ የነበሩት አጼ ምኒልክ ቴሌፎንን ወደ አገራችን ባስገቡ ከአራት ዓመት በኋላ ያስገቧት ነች። መጀመሪያ አለማማጃቸው፤ ከዛም እሳቸው፤ ከዛም ሾፌራቸው የነበረው ህንዳዊው ኤዳልጂ የነዷት መኪና ታወጣው የነበረ በካይ - ለምሳሌ ካርቦን-ዳይ-ኦክሳይድ - የአዲስ አበባን ንጹህ አየር በመቀላቀል አሃዱ ያለ አውቶሞቢላዊ በካይ ሆነ - የአገራችን የአካባቢ ብክለት ታሪክ ቅምሻ

Sunday, August 14, 2011

የምር አቀንቃኞች


(ጌታቸው አሰፋ) በወቅቱ እሠራበት የነበረው የባህርዳር ዩኒቨርስቲ ገና መጀመሩ ነበር - እንደ ዩኒቨርስቲ። ከመደበኛ ሥራዬ ውጪ የአካባቢና የተፈጥሮ ሀብት ጉዳይ የሚገደን ሰዎች ተሰባስበን ክልላዊ የአካባቢ ጥበቃ ጉዳዮች ላይ ግንዛቤ በማስጨበጥ ሥራዎች ላይ የሚያተኩር መንግሥታዊ ያልሆነ ማኅበር አቋቁመን መንቀሳቀስ ጀመርን።እኔ የማኅበሩ ጸሐፊ፤ በግብርና ቢሮ የሚሠራ ሌላ ባለሙያ ደግሞ ሰብሳቢ ሆነን ነበር።  በወቅቱ የባህርዳር ዩኒቨርስቲ ለበርካታ ዓመታት በፓሊቴክኒክነት የቆየውን ግቢ ወደ ቴክኖሎጂ ፋኩልቲ ደረጃ ለማሳደግ አስፈላጊ የነበሩ ግንባታዎችን በስፋት እያጧጧፈ ነበር። ግቢው ቀድመውኑም ቢሆን በጣም ሰፊ ነበርና የቦታ ጥበት አልነበረውም። ይሁንና እስካሁን ድረስ በማይገባኝ ምክንያት ነባር ዛፎች እየተቆረጡ  የነበሩበት ቦታ ላይ ህንጻዎች መተካት ጀመሩ። አንዳንዶቹ ዛፎች የማስፋፋቱ ሥራ ከመጀመሩ ከሠላሳ አራት ዓመታት በፊት ከተቋቋመው ፓሊቴክኒክ ግቢ በላይ እድሜ-ጠገብ ነበሩ።

Wednesday, July 27, 2011

የነፍስ ቁርጥማት


(ጌታቸው አሰፋ)ድርቅ አጥቢያዊ መነሻና ምክንያት አለው። አሁን አሁን ደግሞ እንደ ሉላዊ አባባሽ ምክንያትና መነሻ የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ(በካባቢ አየር ሙቀት መጨመር የሚገለጸው) ይጠቀሳል። ኢትዮጵያ ውስጥ ድርቅ መከሰት የጀመረው የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ሰውኛ መንስኤው ይበልጥ እየተረጋገጠ ከመምጣቱ ቢያንስ መቶ ዓመታት በፊት ነው። በመፍትሔ ደረጃ አጥቢያዊ መነሻው ላይ ስናተኩር የሚጨበጥ ነገር ማድረግ እንችላለን። ሉላዊ መነሻችን እንደ አገር ብቻችንን በተናጠል ከኃሌ-ኵሉ ሆነን የምንፈታው አይደለምና። በዛ ላይ አጥቢያዊ ምንጩን ስናደርቅ ሉላዊ ድርሻችንን ተወጣን ማለት ስለሚሆን አሪፍ ነው።
ለእውቀት ያህል ግን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ በአንዳንድ ቦታዎች ድርቅን ሲያባብስ  በሌሎች ቦታዎች ደግሞ የጎርፍ መጥለቅለቅን ያመጣል (ሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ)። 

Wednesday, July 13, 2011

“እቃሻሻ”

(ጌታቸው አሰፋ)(ደረቅ) ቆሻሻን የሆነ እቃ የቅርብ ዘመድ አድርገን ልንቆጥረው እንችላለን። ዝምድናው በተለያየ መልኩ ሊገለፅ የሚችል ነው። የእቃው አያቶች የሆኑትን ጥሬ ዕቃዎች ከማልማት ሂደት ጋር የሚገኝ ቆሻሻ አለ። እቃው ሲመረት የሚፈጠርም አለ። እቃው ጥቅም ላይ ሲውልም በማርጀት ወይም በመበላሸት ወይም ተጠቃሚው በሌላ ምክንያት እቃውን መጠቀም ሲያቆም የሚፈጠረውም ሌላው ነው።
የቆሻሻ መጥፎነት  - መጥፎ ከሆነ - ከመጠኑና ከይዘቱ ጋር የሚተሳሰር ነው። “ቆሻሻህን አሳየኝና ማንነትህን እነርግርሃለሁ” የሚል አባባል አለ ሲባል ከሰማን ኖረም አልኖረም አባባሉ ትክክል ስለሆነ የለም ብለን ባንከራከር ይሻላል።

Wednesday, June 29, 2011

የችጋርን ቀለበት ሰበራ


(ጌታቸው አሰፋ)ቀለበት የቱ ጋ እንደሚጀምር ለማወቅ ያስቸግራል። እንደ ቀለበት እንዲቀጥል የምንፈልገው በጎ ቀለበት ከሆነ የትስ ቢጀምር ምን ገዶን። መሰበር ያለበት ክፉ ቀለበት ከሆነ ግን የቱ ጋ ነው የጀመረው የሚለውን ጥያቄ መመለስ ወሳኝ ነው። የአገራችን አካባቢ ጉስቁልና እንዲያገግም ለማድረግ በየጊዜው የተለያዩ እርምጃዎች ተወስደዋል።  እየተወሰዱም ነው። ተፈላጊው ውጤት በምንመኘው ልክና ጥራት ግን ለማየት አልቻልንም - እስካሁን። የዚህ እንቆቆልሽ  ቁልፍና የችግራችን መፍትሔ የሚያያዘው የችግሩን ክፉ ቀለበትነት ከመገንዘብ ጋር ነው።  

Wednesday, June 15, 2011

የሚደላን ማመቻመች

(ጌታቸው አሰፋ) ለዛሬ ስለመሬት እጽፋለሁ። ኢትዮጵያችን እንደ አገር ምን ምን እንደሚያስፈልጋት የታወቀ ነው። በራሷ አቅም ህዝቧን መመገብ፤ የውጪ ምንዛሪ ምንጮችን ማስፋት፤ ለዜጎችዋ ቁጥረ-ብዙ የሥራ እድልን መፍጠር፤ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ለማበልጸግ የሚያስችሉ እድሎችን መፍጠርና መጠቀም አለባት። እነዚህን በአጥጋቢ መጠንና ጥራት ማድረግ ያለመቻልዋን የሚያሳብቁ ነባራዊ ተግዳሮቶችን ለመግጠም አገራዊና ዓለም አቀፋዊ ክስተቶች ግንዛቤ ውስጥ መግባት አለባቸው። በተለይ በዓለም ገበያ ላይ ጥገኛ ከመሆን አልፈን የዓለም ገበያን እኛ ላይ ይሄ ነው በሚባል ደረጃ ጥገኛ ለማድረግ ያልቻልን እኛና መሰል አገሮች ዓለም አቀፋዊ የለውጥ ዜማዎችን ተከትለን እስክስ ማለታችን የግድ ሆኗል።