Sunday, November 25, 2012

በ2004 ዓ.ም.ጣራ ስር


(ጌታቸው አሰፋ፤ መስከረም 11  ቀን  2004 ዓ.ም.) እነሆ 2004 ዓ.ም. አለቀ።  ዓመቱን ከኢትዮጵያና ከዓለም የኃይልና የአካባቢ ጉዳዮች አኳያ በግርድፉ እንቃኘው።

‘ብርቱው የአፍሪካ ተደራዳሪ - አፍሪካ በበርካታ ግንባሮች ታጣዋለች።’


(ጌታቸው አሰፋ፤ መስከረም 4  ቀን  2004 ዓ.ም.) በዚህ ሳምንት በሞት የተለዩንን ክቡር አቶ መለስ ዜናዊን ከአዛላቂ ልማት አኳያ የነበራቸውን ሚና በጥቂቱ በማንሳት አስባቸዋለሁ።እንደአለመታደል  ሆኖ እሳቸውም ሳይጽፉ ስላረፉ ወይም በሌሎች ስለሳቸው የተጻፉት ነገሮችም ቢሆኑ በስልጣን ላይ በነበሩበት ዘመን የዕለት ተዕለት ውሎዋቸውን በሚያሳይ መልኩ በዝርዝር አይደለም። እናም ይህን ስጽፍ የምጠቀምባቸው ምንጮች በስራ ዓለም ካወቅኋቸው አጋጣሚዎች በመነሳት ነው።

ስለጅምላ በጅምላ ለጅምላ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ጳጉሜን 3  ቀን  2004 ዓ.ም.) አዲስ አበባ በጣም ሰፍታለች። በርካታ መንገዶች ተሰርተዋል እየተሰሩም ነው - በማሳለጫዎችና በመሽሎኪያዎች እንዲሁም በመንገደ-ብዙ ድልድዮች እየተደገፉ ነው። የመኪኖች ቁጥርም እንዲሁ። የመጓጓዣ ችግር ግን አሁንም እንዳለ ነው። በቁጥርና በጥራት የሚገለጽ። በተለየ በተወሰኑ መስመሮችና ጊዜያት። የየራሳቸውም ሆነ የየመስሪያቤታቸው መኪኖች ከሚያሽከረክረውና  በአንጻራዊነት ጥቂት ከሚባለው የአዲስ አባባ ነዋሪ ውጪ ያለው ሰው ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ራሱንና ቁሱን ለማጓጓዝ የሚጠቀመው በጅምላ መጓጓዣዎች ነው። የጅምላ መጓጓዣ ውስጥ ውይይት ታክሲዎች፤ ሚኒ ባስ ታክሲዎች፤ ከኮንትራት ውጪ የሚሰሩ ትንንሽ ታክሲዎች፤ ሎንቺናዎች፤ የአንበሳ አውቶብሶችና የሃይገር አውቶብሶች ይካተታሉ። በቅርቡ በአዲስ አበባ ስራው የተጀመረው የቀላል ባቡር መጓጓዣም የዚህ ክፍል ዋና አካል ነው።

ክረምትና በጋ


(ጌታቸው አሰፋ፤ ነሐሴ 19  ቀን  2004 ዓ.ም.) የአገራችን የደንና አረንጓዴ ሽፋን ጉዳይ ክረምት ክረምት ሲታይ አማን ይመስላል።  ለወትሮው ራሰ በራ የሚመስለው የሰሜኑ ሜዳና ሸንተረርም ሳይቀር በስሱም ቢሆን በአረንጓዴ ቀለም የተቀባ እንዲመስል የሚያደረገው ክረምት ነው።  ክረምት ከበጋ አገር ምድሩ ሁሉ አረንጓዴ ማድረግ እንኳን ባይቻል እና ባይጠበቅም ቢያንስ ትንሽ የማይባል የአገሪቱ ክፍል ወጥ የሆነ የደንና የሌላ አረንጓዴ ሽፋን እንዳይኖረው የሚደረግበት ምክንያት ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም። ውኃና አልሚዎችን እስካለን ድረስ ይቻላል።

‘በረከተ መርገም’

(ጌታቸው አሰፋ፤ ነሐሴ 12  ቀን  2004 ዓ.ም.) ርዕሱን የተዋስኩት ተወዳጁ የስቶክሆልሙ ኃይሉ ገብረዮሐንስ ወይም ኃይሉ ገሞራው ከዛሬ አርባ አምስት ዓመታት በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ በነበረበት ወቅት ከጻፈውና  ‘በረከተ መርገም’  የሚል ርዕስ ከነበረው ግጥሙ ነው። ኃይሉ ገሞራው ደራሲ፤ገጣሚና ባለቅኔ ነው።  በ‘በረከተ መርገም’ ያኔ ድሮ ያኔ በዓለማችን በተለያየ ዘመን በተለያየ ቦታ ስለ ተፈለሰፉት የቴክኖሎጂ ውጤቶች አንድ በአንድ ፈልሳፊዎቹንም እያነሳ ከተፈጠሩበት ዓላማ ጀርባ ስላላቸው ወይም ሊኖራቸው ስለሚገባው ኅብረተሰባዊ ጠቀሜታ እየጠቆመ ቴክኖሎጂ  በአግባቡ ስንጠቀምበት በረከት ነው በድሃውና በሀብታሙ፤ በተማረውና ባልተማረው፤ በከተሜውና በገጠሬው፤ ‘ባለው’ እና ‘በሌለው’ መካከል ሰፊ ልዩነት የሚፈጠርና ልዩነቱንም በጣም እያሰፋ የሚሄድ ከሆነ  ደግሞ መርገም ነው ይላል። በኃይሉ ገሞራው ‘በረከተ መርገም’ የትችት ስለት የሚተለተሉት በኅብረተሰባዊ ክፍሎች መካከል ያለን ልዩነት በማስፋት አንዱ ወገን ለሌላው ወገን ባርያና አገልጋይ እንዲሆን የሚያደርገው ቴክኖሎጂ ብቻ ሳይሆን ቴክኖሎጂውን የፈጠረውም ሰው ጭምር ነው። 

ከአይበሰብሴው ከረጢት ወደ ዘንቢል- ዘንበል


(ጌታቸው አሰፋ፤ ነሐሴ 5  ቀን  2004 ዓ.ም.) በካናዳ ቶሮንቶ ከተማ በቅርቡ የፕላስቲክ ከረጢት መጠቀምን የሚከለክል ህግ ወጣና መነጋገሪያ ሆነ - በጥቅሙና ጉዳቱ ዙሪያ።  ይህ ከመሆኑ ከአምስት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ስስ ፌስታሎችን የሚከለክል ህግ አወጣች። በየካቲት 5 1999 በነጋሪት ጋዜጣ ላይ በወጣውና አዋጅ ቁጥር 513/1999 ተብሎ በሚታወቀው ይህ ‘የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ አዋጅ’ አንቀጽ ስምንት ንዑስ አንቀጽ 1 እስከ 3 ላይ የፕላስቲክ ከረጢቶች በተመለከተ እንዲህ ይላል፤

‘አዲስ አበባን ያጸዳ የጸዳ ዋጋ ከአምላኩ’


(ጌታቸው አሰፋ፤ ሐምሌ 28  ቀን  2004 ዓ.ም.)ሰኔ ላይ አንስተነው ወደነበረው የአዲስ አበባ ጽዳት ጉዳይ ተመልሰን መጥተናል። የጽዳት ስራውን የሚፈጽም፤ ክትትል ለሚያደርግ፤ የተሻሉና አዳዲስ አዛላቂ ሃሳቦች የሚያፈልቅ የሰው ኃይል ያስፈልጋል። እዚህ ላይ ነው እንግዲ አብያተ እምነት የሚመጡት - የተከታዮቻቸውን የጊዜ፤ የጉልበት፤ የእውቀትና የገንዘብ ሀብት ይዘው። አዲስ አበባ ውስጥ ያሉት አብያተ እምነት ቁጥራቸው በርካታ ነው። አነሰም በዛም በየቤተ እምነቱ በመደበኛነት የሚገለገለው ተከታይ ቁጥር ጠቅላላ ድምር ቀላል አይደለም - ኢመደበኛውን ሳንቆጥር።